Wednesday, 7. January 2009, 12:57:18
ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን
ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው። እራትም ሲበሉ ዲያብሎስ በስምዖን ልጅ በአስቆሮቱ በይሁዳ ልብ አሳልፎ እንዲሰጠው አሳብ ካገባ በኋላ፥ ኢየሱስ አብ ሁሉን በልጁ እንደ ሰጠው ከእግዚአብሔርም እንደ ወጣ ወደ እግዚአብሔርም እንዲሄድ አውቆ፥ ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤ በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ። ወደ ስምዖን ጴጥሮስም መጣ፤ እርሱም። ጌታ ሆይ፥ አንተ የእኔን እግር ታጥባለህን? አለው። ኢየሱስም መልሶ። እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፥ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ አለው። ጴጥሮስም። የእኔን እግር ለዘላለም አታጥብም አለው። ኢየሱስም። ካላጠብሁህ፥ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም ብሎ መለሰለት። ስምዖን ጴጥሮስም። ጌታ ሆይ፥ እጄንና ራሴን ደግሞ እንጂ እግሬን ብቻ አይደለም አለው።
ኢየሱስም። የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፥ ሁለንተናው ግን ንጹሕ ነው፤ እናንተም ንጹሐን ናችሁ፥ ነገር ግን ሁላችሁ አይደላችሁም አለው። አሳልፎ የሚሰጠውን ያውቅ ነበርና፤ ስለዚህ። ሁላችሁ ንጹሐን አይደላችሁም አለው። እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ፥ እንዲህም አላቸው። ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን? እናንተ መምህርና ጌታ ትሉኛላችሁ፤ እንዲሁ ነኝና መልካም ትላላችሁ። እንግዲህ እኔ ጌታና መምህር ስሆን እግራችሁን ካጠብሁ፥ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ እግራችሁን ትተጣጠቡ ዘንድ ይገባችኋል። እኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ባሪያ ከጌታው አይበልጥም። መልእክተኛም ከላከው አይበልጥም። ይህን ብታውቁ፥ ብታደርጉትም ብፁዓን ናችሁ። ዮሐ 13፥1-17 ...............
እርሱም በቢታንያ በለምጻሙ በስምዖን ቤት በነበረ ጊዜ፥ በማዕድ ተቀምጦ ሳለ፥ አንዲት ሴት ዋጋው እጅግ የከበረ ጥሩ ናርዶስ ሽቱ የመላበት የአልባስጥሮስ ቢልቃጥ ይዛ መጣች፤ ቢልቃጡንም ሰብራ በራሱ ላይ አፈሰሰችው። አንዳንዶችም። ይህ የሽቱ ጥፋት ለምንድር ነው? ይህ ሽቱ ከሦስት መቶ ዲናር በሚበልጥ ዋጋ ተሽጦ ለድሆች ሊሰጥ ይቻል ነበርና ብለው በራሳቸው ይቈጡ ነበር፤ እርስዋንም ነቀፉአት። ኢየሱስ ግን እንዲህ አለ። ተዉአት፤ ስለ ምን ታደክሙአታላችሁ? መልካም ሥራ ሠርታልኛለች። ድሆች ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ይኖራሉና፥ በማናቸውም በወደዳችሁት ጊዜ መልካም ልታደርጉላቸው ትችላላችሁ፥ እኔ ግን ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር አልኖርም። የተቻላትን አደረገች፤ አስቀድማ ለመቃብሬ ሥጋዬን ቀባችው። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ወንጌል በዓለሙ ሁሉ በሚሰበክበት በማናቸውም ስፍራ፥ እርስዋ ያደረገችው ደግሞ ለእርስዋ መታሰቢያ ሊሆን ይነገራል።
ከአሥራ ሁለቱም አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ አሳልፎ ሊሰጠው ወደ ካህናት አለቆች ሄደ። ሲሰሙም ደስ አላቸው ብርም ይሰጡት ዘንድ ተስፋ ሰጡት። በሚመች ጊዜም እንዴት አድርጎ አሳልፎ እንዲሰጠው ይፈልግ ነበር። ማር 14፥ 3-11 ...............
መንበረ ጸባኦት ቅድስት ስላሴ ካቴድራል
Monday, 5. January 2009, 21:27:25
የምስጋና ቅኔ በፊትህ ለማቅረብ፣
ማለፍ ነበረብን አስፈሪውን ወጀብ፣
አንተ ብትረዳን አንተ ብታግዘን፣
ታይተው ነበር ጠፉ ከመባል አዳንከን።
የትኛው ግብራችን ከሞት አተረፈን ፣
ቸርነትህ እንጂ በሕይወት ያቆየን።
መንገድ ስተን ወጥተን ተጋልጠን ለአደጋ፣
ማዕበል ወጀብ ገጥሞን እጅግ የሚያሰጋ፣
ድንግል ከለለችን ግርማ ሞገስ ሆና፣
ስሟን ጠርተን አንዴም አላፈርንምና።
በመከራው ሰዓት በዚያ ጭንቅ ቦታ፣
ስምሽን ጠራን ድንግል ስምህን ተራን ጌታ።
ጩኸት ሲበረክት ደጃፉ ተዘግቶ፣
ለጸሎት በረታን አፋችን ተከፍቶ።
አይዟችሁ ለማለት ወገን ሳይመጣልን፣
ባእዳን ደርሰው ነው የተንከባከቡን።
አባት በዚያች ሰዓት እንዲያ ስንሸበር፣
እጅ እግር እያለን ከብዶን መዘዋወር፣
የላካቸው ሰዎች ፈጥነው ደረሱልን፣
ዝማሬው ሲጀመር በሩን ከፈቱልን።
የደረሱት ሰዎች ተጨንቀው በብርቱ፣
አስክሬን ፍለጋ ደጃፉን ሲከፍቱ፣
አፋችን ሲናገር ስንራመድ አይተው፣
እጅግ ተደነቁ ማመን ተሳናቸው።
በሰው ግምት ሞትን <አይተርፉም> ተብለን፣
አንተ ግን ጠብቀህ ለምስጋና አቆምከን።
በአውድ ምሕረት ቆመው ስምህን የጠሩ፣
<ወሮታህ ብዙ ነው> ብለው የዘመሩ፣
የማዳንህን ነገር ጥበቃህን አይተው፣
የደስታ ለቅሶ አነቡ ተቃቅፈው።
የመጣው አደጋ ድንገት የደረሰው፣
ሥልጣን አልባ ነበር በጁ ሞት የለሌለው።
መስኮት ገነጠለ መስተዋት ሰበረ፣
የነበረው ሥልጣን ይህ ብቻ ነበረ።
ነፍሳችንን አዳንክ መጡ መላእክትህ፣
ከአደጋ ከለሉን ዳኑ አገልጋዮችህ።
ፈጣን ተሽከርካሪ እንዲያ እየበረረ፣
ኃይሉን ቀጥ አድርገህ ውሃ ይዞት ቀረ።
ተዓምርህ ጀመረ ዛሬም እንደ ትናንት፣
ለኛ ስብከት ሆነ የማዳንህ ብሥራት።
ከባዱን አደጋ በእለተ እስጢፋኖስ፣
ቀላል አደረግኸው ድል ነሳን ክርስቶስ።
የጨበጥነው መሪ መች አስተማመነን፣
አንተ ፈጥነህ ደረስክ ምድሪቱ ስትክደን
ድንቅ አደረግህልን ተዓምርህን አየን፣
በሣቅ ተቀየረ የነበረን ኅዘን።
በምድረ በዳው ላይ ክብርህ ተገለጠ፣
ከሞት አተረፍከን ታሪክ ተለወጠ።
ለቅሷችንን በሳቅ ኅዘኑን በደስታ፣
የእስራኤል ቅዱስ ለወጥክልን ጌታ።
<አለቀ አበቃለት ተቆረጠ> ሲባል፣
እጅህ ካረፈበት ዳግም ይቀጠላል።
ቸር አባት ነህና እንዲህ ነፍስ ይዘራል፣
እንኳን የወደቀው የሞተው ይነሣል።
ሰምተን ነበር አየን ድንቅ ታደርጋለህ፣
እግዚአብሔር በወጀብ በአውሎ መንድ አለህ
ከቁጥር ሳንጎል እንደወጣን ሳንቀር፣
ልንመሰክር ቆምን የክብርህን ነገር።
ታይተው ነበር ጠፋ መባሉ ቀረና፣
እግዚአብሔር በፊትህ ቆምን ለምስጋና።
ታላቅ መልእክት አለ ያስተላለፍክልን፣
ምሥጢር ገላጭ አምላክ ምሥጢር ግለጽልን
ይህ ነው ልመናችን አምላካችን ስማን፣
ከሕይወት ገበታ ከቤትህ አታውጣን።
ሳንዘጋጅ አይሁን ያ የመምጫህ ሰዓት፣
አብቃን ለንስሃ እግዚአብሔር የኛ አባት።
የማይቀር እንግዳ ስሙ <ሞት> የሚባል፣
ባልታሰበ ሰዓት በድንገት ይመጣል።
ጥሪ ደርሶን ነበር ቀን ሲመሽ በማታ፣
አዳነን ክርስቶስ የድንግል ልጅ ጌታ።
ከደም መፍሰስ ዳንን ከአጥንት ስብራት፣
ከኛ ጋራ ብትሆኝ የአማኑኤል እናት።
የእናትነት ፍቅርሽ ድንግል ሆይ ደረሰን፣
ምልጃ ቃል ኪዳንሽ ከሞት አተረፈን።
ቤትሽን ለመርገጥ እድል ያድረሰን፣
ፈተናው በዝቶብን ከመንገድ የቀረን፣
ዳግም እንመጣለን ቤትሽ ለመሰብሰብ፣
ስምሽን እየጠራን ምስጋና ለማቅረብ።
ቃል ገብተናል ዛሬ ቃል ጠባቂ ያርገን፣
ምስጋና ለማቅረብ ከበሮውን ይዘን።
የበረቱት ልጆች ወጀቡን ሳይፈሩ፣
ለምስጋና ደርሰው በቤትሽ ዘመሩ።
ታላቅ ምስጋና ነው ዛሬ የምናቀርበው፣
በእግዚአብሔ ጥበቃ ከሞት የተረፍነው።
ቤተ እግዚአብሔር ቆመው ላሰቡን አባቶች፣
ለተጨነቁልን ላነቡት እናቶች።
መሥዋዕት ለከፈሉት ወንድሞች እህቶች፣
አዝነው ላለቀሱት ለክርስቶስ ልጆች።
ሁሉንበአንተ አለፍነው ሁሉን አንተ አርገኻል
ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ይገባኻል።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አብርሃም ሰሎሞን የካቲት 25/1999
Thursday, 1. January 2009, 07:16:51
ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ
ሮሜ.12፡11
ክርስትና ከኢየሩሳሌም ውጭ በሌሎች የሮማና የግሪክ ግዛቶች እንደተስፋፋች በተለያዩ የዓለም ክልል ይኖሩ ለነበሩ ክርስቲያኖች በርካታ መልእክታትን በመላክ ያስተምርና ይገስጽ የነበረው ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ በሁሉም መልእክቶች ውስጥ ሥራ የክርስቶስ ተከታዮች የወንጌልና የማህበራዊ አገልግሎታቸውክፍል እንደሆነ ጽፏል። ወደ ሮሜ በላከው መልእክቱም በዚያ ለነበሩ ክርስቲያኖች ለሥራ አትለግሙ ብሏቸዋል። መልእክቶቹ በጊዜው በነበሩ ሰዎች ስም ይላኩ እንጂ አስተማሪነታቸው መጋቢነታቸው እና አስፈላጊነታቸው እስከ ዓለም ፍጻሜ በየትም ቦታ ለሚኖሩ ምዕመናን ስለሆነ ዛሬም ልንመክርባቸውና ልንገለገልባቸው ይገባል። የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ሥርዓትም የተመሠረተው በነዚህ ህያው መልእክቶች ጭምር በመሆኑ እንደ መመሪያ ትጠቀምባቸዋለች። የልማት እንቅፋት የስንፍና አስተማሪ እና የእድገት ጠላት የሆኑ ልማዶችንም ትቃወምባቸዋልች።በትምህርቷ ጸንተው የሚኖሩ ልጆችዋንም ትመክርባቸዋለች።
ሐዋርያው ወደ ሮሜ ከላክው መልእክቱ ሌላ ለቆሮንቶስ ሰዎችም ሲልክ ምእመናንን ማገልገል የተሰጠው ሥራ መሆኑን በመግለፅ እናንተ ሥራችን ናችሁ ሲል /1ቆሮ.9፡1/ ይህም ዋጋን የሚያሰጠው መሆኑን ሲገልጽ የሥራውን ዋጋ ደግሞ እንደ ሥራው መጠን እንደሚመዘን ብዙ የዘራ ብዙ ያገኛል። አበርክቶ የዘራ ብዙ መክር ያፍሳል በማለት /2ቆሮ.9፡1/ ገልፆላቸዋል። ሳይለግም ተግቶ የሠራ የትጋቱን ዋጋ እንደማያጣ አስተምሯል። ስለዚህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህን መሠረት አድርጋ የሥራ የሆነ ሀብትን ያለ ብዙ ድካም በአቋራጭ በዝርፊያና በጉቦ ወይም በግፍ የምናገኘው አለመሆኑን ታስተምራልች። ዛሬ ዓለም ድንቅ የታሪክ ዝክር የሆኑ የሥነ ጽሑፍ፣ የሥነ ሥዕል እና የሥነ ሕንፃ ቅርሶች ባለቤት የሆነችውም እንዲህ ባለ ትምህርት ወልዳ ያሳደገቻቸው ቅዱሳን ሊቃውንት፣ መነኮሳትና፣ ነገስታት ቀን በበጎ ተግባረ እድ ሌሊት በጸሎትና በስግደት ደክመው ያቆዩት መሆኑን ከምስክር ጋር ጽፋ በተግባር ታስተምራለች።
የክርስቶስን ስም ለአሕዛብ የሚሸከም የተባለው ሐዋርያ በቅዱስ መጽሐፉ በሦስተኛ ቅደም ተከተል በተቀመጠው የገላትያ መልእክቱ መጀመሪያ /በገላ.5፡19/ ሥራን ክፉና በጎ /አፍራሽና ገንቢ/ መንፈሳዊና ሥጋዊ/ ብሎ ከፍሎ ካስረዳ በኋላ እያንዳንዱ ሰው የሌላውን ሸክም ከመሸከሙ በፊት የራሱን ሥራ ኃላፊነት ወይም ሸክም መወጣት እንዳለበት ተናግሯል። አንድ ሰው መሥራት እየቻለ በሌላው ትከሻ መኖር እንደሌለበት <እያንዳንዱ የራሱን ሸክም ይሸከም> በማለት መክሯል። /በገላ.6፡4-8/። ሐዋርያው በዚሁ መልእክቱ ላይ እንደገለጸው ክፍያችን እንድሥራችን መጠንና ዓይነት መሆኑን ሲሆን <ሰው የዘራውን ያንኑ ያጭዳል> በማለት ተናግሯል። ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ መሠረት በማድረግ ተግተን በእውነት ብንሠራ ሕይወትን እንደምናገኝ ሰነፎችና ልግመኞች ብንሆን ወይም ክፉ ብንሠራ ደግሞ ወንጀለኝነትና ስደትን፣ ፍርሃትን፣ ሞትን ከሁሉ በላይ ደግሞ ድህነትን እንድምናተርፍ ታስተምራለች።
ረሀብተ መልእክት የተሰጠው ቅዱስ ጳውሎስ የኤፌሶንን ሰዎች ሲመሰክር ፍጹምነት የሚገኘውና በጎ ምኞታችን በትክክል የሚሳካው በሥራ መሆኑን ገልጾላቸዋል። /ኤፌ.4፡12-9/። በበጎ ሥራ የተጉ የፊሊጲስዮስ ሰዎችም እግዚአብሔር የሚሠራው በእናንት ነው> በማለት ነግሯቸዋል።/ፊሊ.2፡12/። የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መምህራንም ይህንኑ መሠረት በማድረግ የማይሠራ ወይም በክፉ ሥራ በተጠመደ ሰው ሕይወት ያለው የአምላክ ሥራ አይገለጽም ከምግባርና ከትሩፋት ከማይርቅ ቀን በጸሎት አንብቦ መጻሕፍት በእርሻ በቁፋሮ ሌሊት በስግደት በአንክሮ በተዘክሮ /የእግዚአብሔርን ሥራ በማድነቅ/ የሚኖር ሰው የእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ ብርሱ ይገለፃል። በእርሱ ላይ መርገሙና ቁጣው ሳይሆን በረከቱና ጸጋው ይታያል። ሰውየውም ሕይወት ያገኛል። በዚህም ዓለም በሚመጣውም ሕይወት በሰው ዘንድ አማላጅ አስታራቂ አባት /እናት/ በእግዚአብሔርም ዘንድ የተመረጠ ባለሟል ሆኖ ይኖራል። ብለው ያስተምራሉ። /ማር ይስሐቅ/። የሚሠራ ሰው ሕይወት አለው። ስለዚህ ሥራ ሕይወት ነው።
ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ሥራን በተመለከተ ጠንከር ያለ መልእክት በላከበት በተሰሎንቄ ጦማሩ ሌትና ቀን ከመትጋት ውጭ ያለች ስንፍናን ፈጽሞ ያወግዛል። ራሱንም አርአያ በማድረግ <ሌትና ቀን በድካምና በጥረት እየሠራን እንኖር ነበር እንጂ ከማንም እንጀራ እንዲሁ አንበላም> /2ተሰ 3፡8/። ብሏል። የተሰሎንቄን ክርስቲያኖች በመጀመሪያ በእጃቸው ሥሩ> /2ተሰ. 4፡11/። ብሎ ያስጠነቀቃቸው ሲሆን በሁለተኛ መልእክቱ ደግሞ <ያልሠራ ከማኅበር አይብላ> ብሎ አዟቸዋል፡፡ ያለ ሥራና ትጋት ከቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ውጭ በየቦታው እየዞሩ የሚኖሩትም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዟቸዋል። /2ተሰ. 3፡10/። በሐዋርያት ላይ የተመሠረተች ሐዋርያት የሰበሰቧት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ በሆነ አገልግሎት ሥራንና የትጋት ሕይወት ትሰብካለች።
ደብራቸውንና በዚያም ያሉት ምእመናንን ትተው በየቦታው እየተዘዋወሩ ለቡራኬ አገልግሎት ለምስጋና የተሸከሙትን ሥልጣን ለልመና መስቀሉን ለማታለያ የሚጠቀሙ ካህናት፤ገዳማቸውን ትተው በከተማ ከወንጌልና ከብሕትውና አገልግሎት ወጥተው በከተማ ተዘርተው በየምእመናኑ ቤት ያለ ሥራ የሚዞሩት መነኮሳት፤ መንፈሳዊ ሕይወት ሥራ አትሥሩ ይመስል በልዩ ልዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶች እያመካኙ ከድካምና ውጣ ውረድ የሚርቁ፤ በሰው ትከሻ የሚኖሩ ምእመናን ጭምር ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያት ሥልጣን አስተላላፊ እንደመሆኗ ከዚሁ ታላቁ ሐዋርያ ግዝትና ማስጠንቀቂያ የወጡ አይደለም። በሐዋርያት ትምህርት የፀናች የተዋሕዶ ሃይማኖት ልጆችዋን ሁሉ በበጎ ሥራ የተጠመዱ ለጽድቅ /ለእውነተኛ/ ሥራ የተጉ እንዲሆኑ ታስተምራለች። እንጂ ስንፍናን ወይም ልግመትን አትናገርም። የቤተ ክርስቲያን አባቶች በየመጽሐፎቻቸው የሚናገሩት ይህንኑ ነው። በመጽሐፈ መነኮሳት መሥራት እየቻለ የማይሠራ ሰው የአጋንንት ማደሪያ፣ የችግርና የክፋት ሁሉ ምንጭ የኃጢውእን ሥራ ሁሉ በተራ ለመሥራት የተጋለጠ ስለሚሆን ሁል ጊዜ ቀን ብቻ ሳይሆን ሌሊቱን እንኳ በትጋሃ ሌሊት እንዲያሳልፍ ያስተምራሉ።
አለመሥራቱም በአንድ በኩል ሕገ እግዚአብሔርን ማፍረስ በሌላ በኩል ደግሞ ለሐዘን መጋለጥ መሆኑን ይናገራሉ። አባ ጊዮርጊስም በሰዓታቱ <እስከ ማእዜኑ አነብር ወስተ ልብየ ትካዜ አሊውየ ሕገ ወትእዛዝ> /አድርግ የተባልኩትን ባለማድረጌ እስከ መቼ ድረስ በትካዜ እኖራለሁ/ በማለት ስንፍና የሚያመጣውን ሐዘን የገለፀበት መጽሐፍ ሁል ጊዜ ይዜማል። ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን ቋሚ ትምህርቷ ሥራ ሕይወት እንደሆነ እና የበረከት፣ የክብር፣የጸጋና የመንግሥተ እግዚአብሔር መውረሻ መሆኑን መግለፅ ነው።
ሥራና የሰው ተፈጥሮ
ሥራ የመርገም ውጤት አይደለም
ሥራ የሰው ልጅ የፈለገውን ነገር በተገቢውና ያለምንም ነቀፌታ የሚያገኝበት ልዩ ተሰጥዖው ነው። ብዙዎቻችን ሥራ ሰው /አዳም/ አታድርግ የተባለውን በማድረጉ ከአምላኩ ጋር ሲጣላ በመረገም የመጣበት የውድቀት ውጤት እንደሆነ ይቆጥራሉ።<ከአንተ የተነሳ ምድሪቷ የተረገመች ትሁን በሕይወት ዘመንህ ሁሉ በድካም ከእርሷ ትበላለህ እሾህና አሜኬላ ታበቅልብሃለች…> /ዘፍ.3፡7/ ያለውን በመያዝ በዚህ ዓለም መቆፈር፣ ማረስና መነገድ የኃጢአትና የመርገም ውጤት እንደሆነ የሚያስተምሩ አሉ።
እውነቱ ግን ሥራ የሰው የተፈጥሮ ሀብቱ እግዚአብሔርንም የሚመስልበት ጸጋው /ስጦታው/ እንደሆነ ነው። ሥራ የሰው ልጅ ሲፈጠር የተሰጠው የመጀመሪያ ሕግ ነው። <እግዚአብሔር አዳምን እና ሔዋንን ፈጠረ።ባረካቸውመ። እንዲህም አላቸው ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት ግዟትም> /ዘፍ.1፡28/።
ለመሆኑ መግዛት፣ ማስተዳደርና መምራት ሥራ አይደለምን? በተጨማሪም አዳም ሳይሳሳት ዕፀ በለስንም በልቶ ሳይረገም እግዚአብሔር አምላክ ገነትን ያበጃጃትም፣ ይጠብቃትም ዘንድ በዚያ አኖረው። ከዚህ የምንረዳው አንደኛ ሥራ የመጀመሪያ ሕግ እንጂ የውድቀት ውጤት አለመሆኑን፣ ሁለተኛ ደግሞ ሥራና ሠራተኛነት እግዚአብሔርን የምንመስልበት ቀዳሚው መስፈርት መሆኑን ነው። በእርግጥ ኃጢአትና ውድቀት የሰውን ልጅ ትጋትና ድካም አክፍተውታል። በቀላሉ ሊሠራው ይችል የነበረውን በብዙ ጥረትና ትጋት እንዲያገኝ አድርገውታል።ልንረዳው የሚገባን ግን ዛሬም ቢሆን በቅንነትና በፍቅር፣ በማስተዋል በእውነት ለሚሠራ ሰው ነገሮች ሁሉ እንደሚሆኑለት ነው።
የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሚጀምረውም የእግዚአብሔርን ሥራ በመዘርዘር ነው። እነዚህም ሥራዎች የአምላክን ክብር የሚገልጹ ናቸው። ሰውም የእግዚአብሔር የእጅ ሥራ ውጤት ነው። ታዲያ ሰው በሥራው እግዚአብሔርን ከመምሰል ሌላ በምን ይመስለዋል? ጌታ ይህችን ዓለም ለሰው ልጅ እንድትመች፣ ከፊሉን ለምግቡ ሌላውን የአምላኩን ሥራ እያሰበና እየተመራመረ የሚያመሰግንበት እንዲሆን አድርጎ በስድስት ቀን ውስጥ ፈጠረ /ሠራ/ በሰባተኛው ቀን ከሥራው አረፈ።ሰውንም እንዲሁ እርሱ የፈጠረው ከላይ መሪና ገዥ ከታች ጠባቂና ተንከባካቢ እንዲሆን አዘዘው። ልክ እንደርሱ ስድስት ቀን ሠርቶ በሰባተኛ እንዲያርፍ ማድረጉ ሥራ ፈጣሪን የምንመስልበት ስጦታ መሆኑን ያስረዳል።ይህንንም ፊልክስዮስ እንዲህ በማለት ገልጾታል <ሰው በሥራው እግዚአብሔር የሚመስል ስለሆነ በትሩፋት ደክመው ለሁሉ በመራራት ጌታን ወደ መምሰል እንዲደርሱ አደረገ።> ብሏል /ፊልክስዮስ ክፍል 9/። እግዚአብሔር ህያው መሆን ነውና፣በሥራ የሕይወት ባለቤቶች እንድንሆን ይገባናል።
ሥራ የደስታ ምንጭ ነው
እግዚአብሔር አምላክ በሥራው ይደሰትና ይረካ እንደነበር ኦሪት <እግዚአብሔር ያደረገው መልካም እንደሆነ አዎ> እያለች ትተርካለች። አዎ ሥራ የደስታ፣ የሰላምና የፍቅር መገኛም ነው። ጠቢቡ <ለሰው ልጅ ከሚበላና ከሚጠጣ በድካምም ደስ ከሚለው በቀር የሚሻለው ነገር የለም።>/መክብብ 2፡24/ ሰው በሥራው ደስ ከሚለው በቀር መልካም ነገር እንደሌለው አየሁ /መክ. 3፡22/ ብሏል። በእርግጥም የሚሠራ ሰው ደስተኛ ነው። የጥገኛነትና የበታችነት ስሜት አይሰማውም። ለያዘው ነገር በስርቆት ወይም በሌላ ነገር ተጠያቂ አይሆንም።የሥራውን ዋጋ የራሱ እንደሆነ ይሰማዋል ቢመጸውት ፍፁም ዋጋ ያገኝበታል። ቢያካፍል ድካሙን ላቡን ወይም ደሙን እንዳካፈለ ይቆጥረዋል። ሌባ ወይም ወንበዴ፣ጉቦኛ በአስበ ደነስ ሀብትን ያጠራቀመ ቢይዘው የሚጥየቅበት የወንጀል ገንዘብ ስልሆነ በፍርሃት ይኖራል። ያለ አግባብ ይበትነዋል። ለጥፋትም ያደርገዋል።ቢያካፍለው ወይም ቢመጸውተው የርሱ ስላልሆነ እውነተኛ ዋጋና ደስታ የለውም። በሥራ የተገኘ ዋጋ ግን ሕይወት ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያለ ድካም የሚገኝ የስርቆት፣ የዝሙትና የኃጢአት ዋጋ <መስዋዕት ዘበአንተ ኃጢአት ኢሠመርኩ> ባለው ቃል መሠረትነት የሥራ ዋጋ አድርጋ አትቆጥረውም።
ዓለም የዝሙትን ዋጋ <ከዝሙት አዳሪነት> የተገኘ /ችጸመመጵረቸፀቷለሰ ስጳ ውጸረከጵረ/ በማለት እንደ ሠርቶ አደር፣ ላብ አደር፣አርብቶ አደር አድርጎ ይቆጥራል። ያንንም ያበረታታል። በሌላ በኩል ደግሞ በሽታ ተስፋፋ ህፅቭ /ጽዕድስ ተዛመተ እየተባለ ይወራል። ዛሬ ሌብነት እንደ ሥራ <ቢዝነስ> እየተባለ ነው። ትንሽ ቆይቶ ሌቦች <ሰርቆ አደር> ጉበኞች <በጉቦ አደር> ይባሉ ይሆናል። የበጎ ሥራ ሰባኪ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ደግሞ አንዳንዶች የልማትና የሥራ እንቅፋት ነች ይሏታል። በእውነት ይህ ተገቢ አይደለምና ሰዎች ለበጎ ሥራ የተነሳሱ ለኅብረተሰቡም ጠቃሚ የሚሆንበትን ነገር በጋራ መፈለግ ይገባል።
ሥራና በዓል
በዓላት በማንኛውም በጋራ በሚኖር እና እርስ በርሱ በሚዋደድ በሚከባበር ኅብረተስብ ውስጥ ልዩ ልዩ ማህብራዊና ሃይማኖታዊ ትርጉም እየተሰጣቸው የሚከበሩ ዕለታት ናቸው። እነዚህ ዕለታት እና ሥርዓታቸው ትምህርታዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጠቀሜታ አላቸው። በቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በዓላት ለብዙ ምክንያቶች ይከበራሉ። ያም ሆኖ ግን አንድም ቢሆን የሥራ እንቅፋትና የእድገት ገች እንደሆኑ ቤተ ክርስቲያን አታስተምርም ። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚከበሩ በዓላት ሁሉ ጌታ ራሱ በሰንበት በጎ ሥራ ተፈቅዷል ባለው መሠረት ነው። ከሰንበት የሚበልጥ በዓል የለም። የሰንበት አከባበርም በሌላው ቀን ለራሳችን ከምንሠራው በተለየ መልኩ ጠዋሪ የሌላቸው አረጋውያን በመደገፍ፣ አሳዳጊ ያጡ ሕፃናትን በመንከባከብ፣ ሕመምተኞችን በመጎብኘት እና በመሳሰሉት በጎ ሥራዎች እንድንፈጽም ቀኖናተ ቤት ክርስቲያን ያዙናል። ቤተ ክርስቲያን ልጆችዋን የምታስተምርባቸው አዋልድ መጻሕፍትንም ብንመለከት ከዚህ የተለየ እውነት አያወሩም።
በድርሳናቱም በገድላቱም የተገለጸው የሥራ ከበሬታና ሕይወትነት ነው።የጌታንም ሆን የቅዱሳንን በዓላት ብናከብር የጌታችን ቸርነት የቅዱሳንን ተጋድሎ ጽናት በማሰብ ስማቸው በመዘከር የሥራቸውን ፍሬ አርአያ እንዲሆነን በመማር ነው። /ዕብ. 13፡1/። የነርሱንም በረከት የምንቀበለው እነርሱ የመሰሉትን አምላክ በመምሰልና በስማቸው ለሌላው በጎ ነገርን በማድረግ በሥራ እየተጋን ነው። ማንም የቅዱስ ሚካኤል በዓል የሚያከብር እርሱ ቁጭ ብሎ ወይም ተኝቶ መልአኩ መጥቶ ዳቦ የጋገረለት ልብስ የሰፋለት የለም። በዓላት የሚከበሩት ክርስቲያን ሠርቶ ካገኘው የታረዙትን አልብሶ የተጠሙትን አጠጥቶ እንዲውል ነው። የደካማን ቤት ጠግኖ፣ የእጓለማውታና የመበልትን እርሻ አርሶ፣ የህሙማን ልብስ አጥቦ አልጋቸውን አንጥፎ ከእነርሱ ጋር አምላኩን እያመሰገነ ነው። ዓለም ደግሞ በዓላትን የሚያከብረው ሰዎች ቁጭ ብለው ቴሌቪዥን ሲያዩ፣ ወሬ ሲያዳምጡ፣በመጠጥና በመዳራት ሌሊቱን ሙሉ ቦግ እልም በሚሉ የጨዋታ ቤቶች ውስጡ ገንዘባቸውን እና ድካማቸውን ከንቱ በመጣል በሥጋም በነፍስም በማይጠቀሙበት ድካም በሽታና ጸጸትን በማትረፍ ነው።
ቤተ ክርስቲያን ግን ይህን አትመክርም። ሥራ ራሱ የደስታ ምንጭ ነው ብሎናል።ከሥራ ውጭ መዝናናትና መደሰት ቢፈልጉም በሌላ በጎ ሥራ በፍቅር ተግባር ደካማውን በማስደሰት በሌላው ደስታ እንዲደሰቱ ትመክራለች።ሐዋርያውም ደስ ከሚለው ጋር ደስ ይበልህ እንዳለ። ታላቁ አባት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሰንበት /በዓላትን/ እንደ ቀድሞ የአይሁድ ልማድ የሚያከብርን ክርስቲያን ያወግዛል። /ሃይማኖተ አበው/ ክርስቲያኖች በዓላትን የሚያከብሩት የሠሩትን ለሌላው በማካፈል ወይም ለሌላው በመሥራት ነው እንጂ የሠሩትን በማጥፋት ዋጋ በሌለው ብክነት አይደለም።
ምግባርና ትሩፋት
ምግባርና ትሩፋት ዘወትር በቤተ ክርስቲያን የሚደጋገሙ ትምህርቶች ናቸው።ቃላቶቹን መግለጽ ቤተ ክርስቲያን ሥራ የሁሉም ክርስቲያን ሕይወት ክፍል መሆኑን የምታስተምርበትን ምስጢር ስለሚያጎላ ትንሽ ማለት እፈልጋለሁ። ምግባር ማለት ማንም ሰው እንደሰውነቱ እንደ ክርስትና አገልግሎት ድርሻው መሥራት ያለበትን ሥራ የሚያጠቃልል ነው። በዚህ ክፍል የታዘዘውን ሁሉ ቢሠራ ደመወዝ ያገኛል። ባይሠራ ይቀጣል። ይህም በዕድሜ፣ በታወቀ ሕመምና በልዩ ልዩ ምክንያት መሥራት ከማይችል በስተቀር ከሁሉም የሚጠበቅ ነው። መሥራት እየቻለ የማይሠራ ሕይወት አይኖረውም። ዋጋም የለውም። ትሩፋት ትርፍ ሥራ ማለት ነው።ዋጋውም እጥፍ ነው። ሰው ከታዘዘው በጎ ሥራ አብልጦ ሌላ በጎ ቢሠራ ትሩፋት ሠራ ይባላል። ይህም ለማስረዳት የሚከተለውን ምሳሌ እንደ አንድ የመንግሥት ሠራተኛ በቀን ስምንት ሰዓት መሥራት አለበት ያም ምግባር ያልነው ነው። ቢሠራ ደመወዝ ይወስዳል። ባይሠራ ይቀጣል። ያለ በቂ ምክንያት ደጋግሞ ካልሠራ ይባረራል። በዛ የሥራ ክፍል ሕይወት አይኖረውም። ትሩፋት ደግሞ ይህን የምግባር ትጋቱን መሠረት አድርጎ የሚሠራው የትርፍ ጊዜ ሥራ ነው /ፕቷረተ ተፀመጵ ወጸረከ/። ምግባር ሳይኖር ትሩፋት የለም ይህም የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘወትር ልጆቻቸውን የሚመክሩበት ቀዋሚ ትምህርት ነው። እኛም አበው ከማንም እንዲሁ / ያለሥራ/ እንጀራ አልበላንም እኛን ልትመስሉ እራሳችንን እንደ ምሳሌ እንሰጣችሁ ዘንድ ነበር። /2ኛ ተሰ. 3፡10 ባሉት መሠረት በትጋትና በጥረት በብዙ ውጣ ውረድ የክብር ባለቤት የሆኑ አባቶቻችንን ትምህርትና ሕይወት ምሳሌ በማድረግ ወገንን እና ሀገርን ለሚጠቅም ክብርንም ለሚያስገኝ ሥራ ሁሉ እንፋጠን። ሥራ ሕይወት ነውና በሕይወት ያለን ሁሉ ዘወትር በበጎ ሥራና ግንባታ ልንኖር ይገባናል። ሥራን መመሪያችን ልናደርግ ያስፈልጋል። የሕይወትና የክብር ባለቤት ሕይወት በሚገኝበት ሥራ እንድንከብር ትጋትን ያድለን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል /መ/ር/
ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ
ጥናትና ምርምር ክፍል
Friday, 12. December 2008, 02:20:56
መጠራታችሁን ተመልከቱ 1ቆሮ.1፡26
በዲ/ን ንዋይ ካሳሁን
ቆሮንቶስ በዘመነ አዲስ መጀመሪያ ከግሪክ ታዋቂ ከተሞች አንዷ ነበረች። በቆሮንቶስ ክርስትናን ሕይወት ያደረጉ ክርስቲያኖች ነበሩና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሁለት መለክታትን ጽፎላችዋል። በመጀመሪያው መልእክቱ የምናገኘው ይህን ኃይለ ቃል ያስተላለፈላችው ስለ ሦስት ምክንያት ነው።
እነዚህም በመካከላቸው ከሚሰማው መለያየት በዘመኑ ሕዝቡ ይታመንበት ከነበረው የዝሙት ተግባር እና አምልኮተ ጣዖት እንዲለዩ ነው።
ሐዋርያው ሁለት መልእክታት የላከላቸው እንዲሁ አይደለም በመጀመሪያው መልእክቱ ተጸጽተው ነበርና ዳግመኛ መልእክት ልኮ ያጽናናቸው ነበር።
የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከልዩ ልዩ ሕይወት የተጠሩ ነበሩና ልዩ ልዩ ሕዝቦች ይኖሩባት የነበረች ከተማ በመሆኗ ለክርስቲያናዊ ሕይወት ምቹ አልነበረችም። በነዚህ እንቅፋቶች እንዳይጥልፉ ነበር ቅዱስ ጳውሎስ <<ወንድሞች ሆይ መጠራታችሁን ተመልከቱ>>ያላቸው።
<<እንደ ሰው ከልብ ጥበበኞች የሆኑ ብዙዎች ኃይለኞችም የሆኑ ብዙዎች ባላባቶችም የሆኑ ብዙዎች አልተጠሩም።ነገር ግን እግዚአብሔር ጥበበኞችን ሲያሳፍር የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ ብርቱውንም ነገር እንዲያሳፍር እግዚአብሔር የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ እግዚአብሔርም የሆነውን ነገር እንዲያጠፋ ምናምንቴ ነገር መረጠ። ሥጋን የለበሰ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት እንዳይመካ ነገር ግን የሚመካ በእግዚአብሔር ይመካ በማለት ሰዎች በተጠሩበት ዓላማ መጽናት እንዲገባቸው አሳስቧል።
የክርስቲያናዊ ሕይወት ጥሪ ደርሶን የመጣን ሁላችን ከየት እንደተጠራንና የት እንዳለን ወዴትም እንደምንሄድ ለምንስ እንደተጠራን ልናውቅ ይገባናል።
ግን ለምን ተጠራን?
ይህንን መልስ የሚሰጠን ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ‘ ኑ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ ’ በማለት የመጠራታችንን ዓላማ ፈሪሃ እግዚአብሔርን እንድንማር መሆኑን ይነግረናል። መዝ. 33 ቁ.11። እግዚአብሔርን መፍራት ደግሞ የጥሪያችን ዓላማ ብቻ ሳይሆን ነብዩ የጥበብ ሁሉ መጀመሪያም እንደሆነ ነግሮናል። መዝ. 7ቁ.1
የያዕቆብ ልጅ ዮሴፍ ሃይማኖትን ከአባቱ ሕይወት የተማረ ነበርና የተጠራበትን ዓላማ በተሰደደበት ሀገርበጲጥፋራ ቤተ መንግሥት ተቀምጦ እንኳን አልዘነጋውም ነበር።የሃይማኖት ሰው ከሃጢአት ጋር የማይተባበረው የተጠራበት የመጀመሪያ ዓላማ እግዚአብሔርን መፍራት ስለሆን ነው። ዘፍ. 8ቁ.9።
ለሕግጋተ እግዚአብሔር መገዛት የማይችሉ ሰዎች ያጡት ታላቀ ጸጋ ቢኖር የመጀመሪያው ፈሪሃ እግዚአብሔር ነው።
ሌላው የተጠራንበት ዓላማ <እረፍት> ነው። ክርስቲያኖቸ በእግዚአብሔር አንድላይ ያረፍን ሰዎች ነን።<ቀና ብላችሁ እንድትሄዱ አድርጌአችኋለሁ> እንዲል።ዘሌ.26 ቁ.13። ኃጢአት አንገታችንን ሰብሮት ነበር፣ ጠላት አሸማቅቆን ነበር፣ ወገባችንን አጉብጦት ነበር። ይሁን እንጂ አምላካችን <እናንት ሸክም የከበዳችሁ ኑ እኔ አሳርፋችኋለሁ> እንዳል የከበደንን ሸክም አቀለለልን። ኢሳ.53፤34። በራሳችን ኃይልና ጉልበት ማስወገድ የማንችለውን ቀንበር አቀለለልን።ማቴ.11፡28፡፡
የክርስትና ጥሪ የዓለምን ቀንበር ጥሎ የእረፍት ምልክት የሆነውን መስቀል መሸከም ነው። ከዚህ በኋላ ነው ሕይወት የእረፍት የምትሆነው።
ክርስትና የ<ደስታ> ጥሪ ነው። ደስታውም የእኛ ብቻ አይደለም እኛ እግዚአብሔርን ደስ የምናሰኝበትና በአምላካችን ደግሞ እኛም ደስ የምንሰኝበት እንጂ። ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት <ኑ በእግዚአብሔር ደስ ይበለን> እንዲል። መዝ.94፡1።
ደስታን ፍለጋ የስው ልጆች ያልቆፈሩት ጉድጓድ የለም። የእውነተኛ ደስታ መገኛው ግን እግዚአብሔር ብቻ ነው። ክርስትና እውነተኛና ዘላለማዊ ደስታን ፍለጋ ወደ እግዚአብሔር መምጣት ነው። <ሁል ጊዜ በጌታ ደስ ይበላችሁ> በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያናዊ ሕይወት ሁል ጊዜ ደስተኛ እንደሆነ ይነግረናል። በማጣትና በማግኘት፣ በጤናና በሕመም…. ሁል ጊዜ የደስታ ሕይወትን ለማግኝት ነው ወደ ሃየማኖት የተጠራነው።
የንጽሕናችን መሠረት ድንግል ማርያም በጸሎቷ ውስጥ እንድናገኘው <ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች መንፈሴም በመድኃኒቴ በአምላኬ ሐሴት ታደርጋለች> በማለት የደስታዋ ምንጭ እርሱ አምላካችን እግዚአብሔር እንደሆነ ነግራናለች።
የእግዚአብሔር መንግሥት ዘለዓለማዊ ነው። የክርስትና ጥሪም የመጨረሻ ግብ ይህን የማያልቅና የማይጠፋ ዘለዓለማዊ መንግሥትን መውረስ ነው። <እናንተ የአባቴ ቡሩካን ዓለም ሳይፈጠር ወደ አዘጋጀሁላችሁ መንግሥት ግቡ> ተብሎ ለሃይማኖት ሰዎች የተነገረው የተስፋ ቃልም በስሙ እንድንጠራ በመንፈስ ወልዶ ያሳደገን በፀጋው ሁሉ የጠበቀን አምላካችን እግዚአብሔር የጠራንም ይህን መንግሥቱን ሊያወርሰን ነው።
ጌታችን በወንጌል እንዳስተማረን ይከተሉት ለነበሩ የአምስት ገበያ ያህል ሕዝብ ባስትላለፈው መልእክት <እናንተ ምግብን ስለተመገባችሁ ተከተላችሁኝ ነገር ግን የዘላለም ሕይወት እንዲሆንላችሁ የሰውን ልጅ ሥጋውንና ደሙን ልትመገቡ ያስፈልጋችኋል>።
ሰው በሥጋ ምግብ ብቻ መኖር አይችልምስለ ነፍሱም ቤዛ ሰማያዊውን መና ደግሞ ሊመገብ ያስፈልገዋል።ዮሐ.6ቁ.54። ስለዚህ የተጠራነው ለነፍስ ምግብ እንድናገኝና ሕይወትም ይሆንልን ዘንድ ነው።
በአጠቃላይ ሐዋርያው ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ባስተላለፈው መልእክት ውስጥ <መጠራታችሁን ተመልከቱ> የሚለው ዐቢይ ቁም ነገር ያነሣው ለመለያየት፣ ለጠብ፣ ለክርክርና ለኃጢአት ሥራ አለመሆኑን ተረድተን የተጠራንበትን ዓላማ እንድንፈጽም ነው።
የተጠራነው ለሐዘንና ለእንባ ሳይሆን ለደስታ ነው፣ ለጸብና ለክርክር ሳይሆን ለመዋደድና ለመከባበር ነው፣ ለኃጢአትና ለርኩሰት ሳይሆን ለጽድቅና ለቅድስና ነው፣ይኸውም ለሕይወት እንጂ ለሞት፣ ለነፃነት እንጂ ለባርነት አልተጠራንምና። ስልሆነም በጎ መጠራታቸንን እናስብ።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
Sunday, 21. September 2008, 20:57:20
ከአዳም ነው ግኝትህዘፍ 1፡ 26- 28ብዙ አውቀናል ስንል ብዙ ተምረናል፣
የጎደለን አለ ገና ይቀረናል፡፡
አንድ የመሆን ነገር እንደ ሻማ ቀልጦ፣
መስማማት ከበደን ከፍቅር ዘር በልጦ፡፡
ብዙና ተባዙ ምድርን ሙሏት ማለት፣
ተዋጉ አልነበረም ይህን እወቅ ፍጥረት፡፡
በሰናኦር ምድር ቋንቋ ቢደባለቅ፣
“ባቢሎን” ተብሎ ከተማ ቢታወቅ፣
ምድሪቱን ቢሞላት ህዝብ ተበትኖ፣
ሃገር ቢከፋፈል ድንበር ተወስኖ፣
ለምን ነው መንደዱ የጸብ የጥል እሳት፣
የሰው ልጅ ለማጥፋት ጦር መምዘዝ ጦር ማንሳት፡፡
ምነው ያዜብ ንግስት ከጦቢያ ተነስታ፣
ሰላም ይዛ መጣች እውቀት ጥበብ አይታ፡፡
የጀግና ዘር ብለህ አትታጠቅ ዝናር፣
መግደል ውርስ አይሆንም እባክህ ሰው ተማር፡፡
ባለንበት ዘመን ጀግንነት ወንድነት፣
ተስማምቶ መኖር ነው በፍቅር ባንድነት፡፡
የሰው ልጅ ከማዳን የሰው ልጅ ለማጥፋት፣
ስንት ጥበበኛ ይጫወታል በእሳት፡፡
ሰው ጥበብ እውቀትህ ችሎታህ ሲለካ፣
ሃብት ያፈሰስክበት ለጥይት ነው ለካ፡፡
በደቂቃ የሚገል መሳሪያ ሲሰራ፣
በደቂቃ የሚድን ምነው አልተሰራ?
ባልተገባ ነገር በማይሆን ተጣልተን፣
አብረን እየበላን ሆድና ጀርባ ነን፡፡
መንገድ ሊያሳስተን ሊያጣላን ከመሲህ፣
ሰይጣን እባብ ሆኖ አይመጣም ከእንግዲህ፡፡
ስንፍናችን ታውቆ ለዘር ማደራችን፣
ሰይጣን ተደላድሎ ገባ መሃላችን፡፡
ሁሉ ፍጡር ሆኖ አምላክ የቀረፀው፣
ነገድ ጎሳ ከፍለህ ምነው ተጣላህ ሰው፡፡
“የእገሌ ! የእገሌ ! “ ሲባባሉ ሰምቶ፣
ሰውን ተከትለው ሲከፋፈሉ አይቶ፣
ሐዋርያ የሚሆን የጌታ ክርስቶስ፣
ይህን ተናገረ እንዲህ አለ ጳውሎስ፡፡
“የ አጵሎስ ነኝ ትላለህ አጵሎስ ምን አረገ፣
የጳውሎስ ነኝ ትላለህ ጳውሎስ ምን አረገ፣
ሰው ቢወጣ ቢወርድ ልቡ እንደፈለገ፣
እግዚአብሔር አይደል ወይ ተክሎ ያሳደገ? “
የተወለድክበት ስፍራው ቢነገርህ፣
የሰው ልጅ መሞቻህ አይደል እንዳሳብህ፡፡
ለመቀራረቡ አብሮ ለመብላቱ፣
“ ሰሜን ደቡብ” መባል ባልከፋ ሰርአቱ፡፡
“ምስራቅ ምዕራብ” ብሎ ለጦር መደራደር፣
ያ ነው ግብዝነት መንገድ ስቶ ማደር፡፡
እንግዳ እየሆነ ሚስጥር አይክበድህ፣
ሐቁን ስማ ፍጥረት እውነት ይኸውልህ፣
በአንተ “ሰሜን” መሆን በአንተ ”ደቡብነት”፣
በአንተ “ምስራቅ” መሆን በአንተ “ምዕራብነት”፣
ምን ይገኛል ብለህ ነገድ ከፋፈልህ፣
የስድስተኛ ቀን የእግዚአብሔር ፍጡር ነህ፡፡
እራስክን ከፍ አታድርግ ከማንም አትበልጥም፣
እራስክን ከፍ አታድርግ ከማንም አታንስም፣
አንተ ሰው ነህ እንጂ አምላክ አይደለህም፡፡
ከ አዳም የተለየ የዘር ግንድ የለህም፡፡
ሰው አንተን ባይመስል ይዘት ቅርፅ አቋም፣
አይን ጥርስ አፍንጫ ጠጉርና ቀለም፣
የጥቁር የነጩ የ ቀይ የጠይሙ፣
እንደ መልኩ አይደለም አንድ አይነት ነው ደሙ፡፡
ወዶ ቀይ አልሆነም ፈልጎ አልጠቆረም፣
ይኸን መርጦ አመጣው እግዚአብሔር ወደ ዓለም፡፡
አንተ አዘኸው አይደል የሰው ጠይምነት፣
እግዚአብሔር ፈቅዶ ነው የመልክን ልዩነት፡፡
ከየት እንደመጣህ ማስተዋል አትርሳ፣
ምነው ዘር ከመሃል ትቆጥራለህሳ?
ከሰሜን አይደለም ትውልድ አመጣጥህ፣
ከደቡብ አይደለም የዘር መሠረትህ፣
ከምስራቅ አይደለም ጎሳና ነገድህ፣
ከምዕራብ አይደለም የሰው ልጅ እርስትህ፣
መነሻ መፍለቂያ የሕይወት ጅምርህ፣
ካፈር ከተሰራው ከአዳም ነው ግኝትህ፡፡
ሰው ክቡር ነህና ማስተዋል ይብዛልህ፣
የሕይወት ባለቤት እግዚአብሔር ይባርክህ፡፡ ያቺን ቀን በጸፍ ጸፍ
/ከሚል መጽሐፍ የተወሰደ/
በአብረሃም ሰሎሞን
ከአዳም ነው ግኝትህ
Friday, 23. March 2007, 20:41:59
“እግዚአብሔር በአንድም መንገድ በሌላም ይናገራል፡፡” ኢዮ. 33 ፡14 ፡፡
ክርስትና ጥላቻን አይሸከምም
ክርስትና የተመሠረተው በፍቅር ላይ ነው፡፡ ያውም ሊተረጎም በማይችል ፍቅር ላይ ፡፡ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ክርስቶስ በመስቀል ላይ በመሠረተው ልዩ ፍቅር ላይ፡፡ የክርስትና መመሪያው “ጠላትህን ውደድ” ነው፡፡ ለዚያውም ክርስቲያን ከዲያብሎስ በቀር ጠላት የለውም፡፡ ግን አንተ ባትጣላውም እርሱ የሚጠላህን፣ አንተ ክፉ ባታደርግበትም እርሱ ክፉ የሚያደርግብህን ውደድ ሲል ነው፡፡
በክርስቲያኖች መካከል ልዩነቶች ባይኖሩ ይመረጣል፡፡ እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው መኖር ቢችሉ ጠላታቸው ዲያብሎስ ያፍራል፣አባታቸው እግዚአብሔር ይደሰታል፡፡ እነርሱም መለያየት ከሚያስከትለው ፈተና ይድናሉ፡፡ ይሁን እንጂ በክርስቲያኖች መካከል መሠረታዊ ያልሆኑና የሆኑ ልዩነቶች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ መሠረታዊ ልዩነቶች የምንላቸው በሃይማኖት የተነሳ የሚከሰቱ ልዩነቶችን ነው፡፡ እነዚህ ልዩነቶች ዲያብሎስ በሰዎች እያደረ በሚዘረው እንክርዳድ ምክንያት ሚከሰቱ ናቸው፡፡ አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት ከሚለው የሐዋርያው ትምህርት የሚወጣ /ኤፌ 4 ፡ 5/፡ እውነትን በመቀበልና ባለመቀበል መካከል የሚደረግ ተጋድሎን የሚያስከትል በመሆኑ ከጥንት ጀምሮ የዚህ ልዩነት ምንጩም፣ አመንጭዎችም ሲወገዙ ኖረዋል፡ ይኖራሉም፡፡
ይህም ቢሆን የተለየው ወገን እንዲመለስ፣ እንዲያምን ይደረጋል፣ ካላመነ ካልተመለሰም ተወግዞ ይለያል እንጂ ይውደም ፣ይሙት፣ ይጥፋ ተብሎ ምድራዊ ቅጣት አይታዘዝበትም፡፡የጠላትነት ስሜት ተፈጥሮ /እንዲፈጠር ሆኖ/ ዓይንህን አልየው ድምፅህን አልስማው አይባልም፡፡ እንኳን በሃይማኖት የሚመለሱ ወገኖቹን ይቅርና ሌሎቹንም የሰው ዘሮች ቢሆን ፍቅር ከማሳየት ውጪ የማጥፋትና የማስወገድ መርህ ለክርስቲያን ሊኖረው አይገባም፡፡ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ከሙስሊም ወገኖቻቸው ጋር በተዐቅቦ ተከባብረውና ተፋቅረው የኖሩት በዚህ መሠረታዊ ትምህርት የተነሣ ነው፡፡ የገዛ ወገኖቻቸው ያሳደዷቸውን የነብዩ መሐመድ ተከታዮች ቦታ ሰጥተው፣ሕይወታቸውን ታድገው፣ለጠላቶቻቸው አሳልፈው ሳይሰጡ የተንከባከቧቸው በዚህ የተነሣ ነበር፡፡
በክርስቲያኖች መካከል መሠረታዊ ያልሆነ ልዩነት ሊኖርም ይችላል፡፡ በዘር፣ በቋንቋ፣ በፖለቲካዊ አመለካከት፣ በሥልጣን ክፍፍል፣ በሀብት ክፍፍል፣ በዜግነት፣ በመልክና በቁመና፣በዕውቀት፣ ወዘተ… መለያየቶች ቢኖሩም እንኳን ክርስቲያናዊ እምነትና ሕይወት አቻችሎ፣ አስማምቶና አዋህዶ ያለበለዚያም ልዩነቶቹን ኅብረ ውበት አድርጎ ቆጥሮ ይጓዛል እንጂ መሠረታዊውን የፍቅር ኑሮ አናግተው ለጥላቻና ለመለያት አያደርጉም፡፡ ክርስትና የተማረውን /ምሁር የሆነውን/ ጳውሎስ ከዓሣ አጥማጅ ጴጥሮስጋር፣ ቀራጩ ማቴዎስን ከሰዓሊው ሉቃስ ጋር፣ ንጉሡ ካሌብን፣ ከገበሬው ዜና ማርቆስ ጋር፣ሮማዊውን ዲዮናስዮስ ከዕብራዊው ቶማስ ጋር፣ግባጻዊውን አትናቴዎስ ከሶርያዊው ከኤፍሬም ጋር፣ ያስተሳሰረች ሠንሠለት ናት፡፡ የዘር ልዩነቶች የክርስትና ኑሮ ውስጥ ከልዩነት አይቆጠሩም፡፡ ስንዴ ለመገበሪያ የሚውለው የት ተዘርቶ በቀለ በሚል ሳይሆን ስንዴው ራሱ ንጹሕ ነው ወይ? በሚለው መመዘኛ ነውና፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በኢትዮጵያ የሚከበሩትን ያህል በግብጽ ይከበራሉ፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከተወለደበት ከልዳ በበለጠ በኢትዮጵያ ይከበራል፣ፍሬምናጦስን በሀገሩ በግሪክ የሚያስታውሰው ባይኖርም ኢትዮጵያውያን ግን ከሣቴ ብርሃን እያሉ ያከብሩታል፡፡
ሰዱቃውያን ፈሪሳውያን ጳውሎስ የአመለካከት ልዩነታቸው ወደ ክርስትና እንዳይመጡ አላደረጋቸውም፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እርስ በርስ ከማይዋደዱት ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት እና ከሰለሞናዊ ሥርወ መንግሥት መካከል ቅዱሳንን ሰይማ ታከብራለች፡፡ ቅዱስ ላሊበላን ቅዱስ ቴዎድሮስን /ወልደ ንጉሥ ዳዊት/ መጥቀሱ ይበቃል፡፡
ፖለቲካዊ አመለካከቶች የርዕዮተ ዓለም ልዩነቶች እንጂ ክርስቲያናዊ ልዩነቶች እና የጥላቻ መንሥኤዎች ተደርገው መወሰድ የለባቸውም፡፡ሶሻሊስቱም፣ ሶሻል ዲሞክራቱም፣ ሪፖብሊካኑም፣ አብዮታዊ ዲሞክራቱም፣ ሌላውም ሌላውም ያላቸውን የአመለካከት ልዩነት ልዩነት አቻችለው በአንዲት ቤተ ክርስቲያን መኖር፣ ማስቀደስ መቁረብ ይችላሉ፡፡ ልዩነታቸው መሠረታዊ አይደለምና ዘርን፣ አመለካከትን፣ ሥልጣንን ወዘተ… መሠረት አድርገው የሚነሱ የጥላቻ ስሜቶችን ለማስተናገድ ክርስተና ቦታ የለውም፡፡ ከባሕሪው ጋርም አይሄድም፡፡ ከቁ ስጥንጥንያ ቤተ መንግሥት የወጣው አርሳንዮስ ከግብጽ ከመጣው መቃርስ ጋር በአንድ ገዳም ኖሯል፡፡ ፍቅር ስላሸነፈ፡፡ ክርስትና እነዚህን ልዩነቶች ድል ነሥቶ የበላይ ካልሆነ የንን ህይወት ክርስትና ነው ማለት ያዳግታል፡፡ አንዱ መለያው ይህ ነውና፡፡ ይህ ወንድሜ አመለካከቱ እንዲሁ ነው፡ እኔ አልቀበለውም ከማለት ባለፈ በዚህ አመለካከቱ የተነሣ አልወደውም፣ እርቀዋለሁ፣ ይጥፋ፣ይሙት በቃ፣ ይወገድ፣ ይውደም የሚለው ዛቻ የተሞላበት አካሄድ ፈጽሞ ክርስቲያናዊ አይሆንም፡፡ ይኸኛው ዘር ይጥፋ፣ ይኸኛው ዘር ይወገድ፣ያኛውን ዘር አትቅረቡ፣ ሌላውን ወገን ውደዱ የሚለው መሥመር ሰይጣናዊ እንጂ ክርስቶሳዊ አይደለም እርሱማ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው ነው ያለው፡፡
በመሆኑም ከክርስቲያናዊ የፍቅር ሕይወት ጋር የሚቃረነው የጥላቻ ስሜት በልቦናችን ድሩን እንዳያደራ፣ ፍሬዎቹን መለያትንና መገዳደልንም /መጠፋፋትን/ በመንፈሳዊው የፍቅርና የመቻቻል ሽቱ እናጥፋው፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
Sunday, 3. December 2006, 00:03:13
ፈለገ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን
Read more...
Wednesday, 29. November 2006, 01:56:58